ውሽት ነገሠ!
Posted by posted on February 04 2010 11:40:27
ዳግማዊ ዳዊት
Extended News

ውሽት ነገሠ!

መስቀል አደባባይ- ሀዝባችን ተጠርቶ

ሕጻን ሽማግሌው ባልቴት እና አዋቂው-

          ግልብጥ ብሎ ወጥቶ

የክብር እንግዶች- ከአውሮጳ ከእስያ

ከጎረቤት ሃገር- ጅቡቲ ኬንያ

የአማሪካው ቆንሲል- ሚስተርም ተገኝተው

ጳጳሱ ተጠርተው- ካህናት ቀድሰው

ቅባ-ቅዱስ ፈልቶ-በአናቱም አፍስሰው

አክሊል ተደፋለት- እምቢልታ ተነፋ

ሕዝብ ሠገደለት- ሥልጣን ክብሩ ሰፋ

ከበሮ ተመታ-ሆታውም ቀለጠ- እልልታ ተሰማ

ውሸት ንጉሥ ሆነ- ሰርቆት አልጋ ወራሽ-በአገሬ ከተማ። 

    እናም የእኛ ሰፈር- ትልቅ ሽማግሌ

    አንቱ የተባሉት- ትናንት እና ዛሬ

    በቁርባን ያገቡት- በክርስትናቸው

    ይኸው በአደባባይ -ሲዋሹ ያዝናቸው። 

መቸ ይኸ ብቻ- ሆነና ነገሩ

በሃሰት ተከስው- ተሰማና ፋይሉ

ደግነት ቅንነት- እስር ቤት ገቡ አሉ። 

    እንግዲህ ምን ይሉ- ዘመን ተቀየረ

    ውሃ ሽቅብ አይፈስ- ሲባልም ነበረ

    ዘመን ተገላብጦ - ውሸት ተከበረ። 

ኑሯችን ሆነና- ከደሃው ቀምተን

እውነትን ንቀነው- ውሸትን አንግሰን

ወደፊት ለመሄድ - መራመድ አቃተን። 


ዳግማዊ ዳዊት

የካቲት 2002 ዓ.ም.